Home ዜና የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ እና የጊዜያዊ አስተዳደሩ ከፍተኛ...

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ እና የጊዜያዊ አስተዳደሩ ከፍተኛ የካቢኔ አባላት በኢትዮዽያ የአሜሪካ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ማሲንጋ ኢርቪን የሚመራ ልኡካን ቡድን ጋር በፕሬዝዳንቱ ፅህፈት ቤት ተወያዩ።

154

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳና ካቢኒያቸው ከአሜሪካ ልኡካኑ ጋር ባደረጉት ውይይት የተነሱ ሃሳቦችን በተመለከተ ለመገናኛ ብዙሃን ማብራርያ የሰጡት የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝደንት ልዩ ረዳት ጎይተኦም ታጠቅ የፕሪቶሪያው ስምምነት በርከት ያሉ አወንታዊ እርምጃዎች የተስተዋሉበት እንደሆነ ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ በአምባሳደር ማሲንጋ ኢርቪን ለተመራው የአሜሪካ ልኡክ ገልፀውላቸዋል ብለዋል።

ቢሆንም ግን የትግራይ ግዛታዊ አንድነት እስካሁን አለመረጋገጡና ወራሪ ሃይሎች አሁንም የትግራይን አካባቢዎች በወረራ በመያዛቸው ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ አለመቻላቸውና በዚህ ረገድ የፌደራል መንግስት ሃላፊነቱ እየተወጣ አለመሆኑ ብሎም ሌሎች ተግባራዊ ያልሆኑ አንኳር የስምምነቱ ነጥቦችም በፕሬዝዳንቱ ለልኡካኑ ማብራርያ እንደተሰጠም ነው አቶ ጎይተኦም የተናገሩት።

በውይይቱ የተነሳው ሌላው ነጥብ ደግሞ በፌደራል መንግስት በኩል እየተባለ ስላለው የሪፈረንደም ጉዳይና የያዘው አቋም ወራሪ ሃይሎች ከተቆጣጠሩት የትግራይ አካባቢዎች ሳይወጡ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ የሚል እንቅስቃሴ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ትክክል አይደለም ብሎ እንደሚያምን ገልጸዋል።

ህዝቡን ያፈናቀሉትና ጨፍጫፊ ሃይሎች ከተቆጣጠሩት የትግራይ አካባቢዎች ሳይወጡና የትግራይ ገዜያዊ አስተዳደር መዋቅሩን ወደ አካባቢው ሳይዘረጋ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ ለደህንነታቸውም አስጊ በመሆኑና ጉዳዩም ግልፅ ባለመሆኑ በዚህ ጉዳይ ላይ ጊዜያዊ አስተዳደሩ የፌደራል መንግስት አቋምን እንደማይደግፍ ጠንካራ አቋም ይዞ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ነው የገለጹት።

ሪፈረንደም ይካሄድ ቢባል እንኳን መሆን ያለበት በህገ መንግስቱ አሰራረ መሰረት በመሆኑ በህዝብ የተመረጠና የህዝብ ተቀባይነት ያለው መንግስት ሳይመረጥ በጊዜያዊ አስተዳደሩ ሊሆን እንደማይችልም በጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ለአሜሪካ ልኡካኑ ገለፃ ተደርጎላቸዋል ብለዋል የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝደንት ልዩ ረዳት ጎይተኦም ታጠቅ።

በፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት መሰረት የትግራይ ሰራዊት ትጥቅ ቢፈታም በዲዲአር ላይ እንደተቀመጠው የሰራዊቱ አባላትን መልሶ ማቋቋምና ወደ ህብረተሰባቸው ተቀላቅለው ኑርዋቸውን ለመምራት በፌደራል መንግስት መደረግ የነበራቸው ስራዎች እንዳልተሰሩ መገለፁንም ተመላክቷል።

በኢትዮዽያ የአሜሪካ አምባሳደር ማሲንጋ ኢርቪን በበኩላቸው የትግራይ ህዝብ ከደረሰበት ችግር እንዲላቀቅና ሙሉ ሰላም አግኝቶ ወደ ልማት እንዲገባ እንዲሁም በኢትዮዽያ ሰላም ልማትና መረጋጋት ይሰፍን ዘንድ ያለን አጋርነት አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ መግለፃቸውን ነው አቶ ጎይትኦም ታጠቅ ያብራሩት።

#በታሪክ ፍሳሃ

All reactions:1919