Home ዜና የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሓኖም ከካዛኪስታን ብሄራዊ የህክምና ሳይንስ...

የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሓኖም ከካዛኪስታን ብሄራዊ የህክምና ሳይንስ ዩኒቨርስቲ የክብር የፕሮፌሰርነት ማአረግ ተበረከተላቸው፡፡

579

ዶክተር ቴድሮስ የክብር የፕሮፌሰርነት ማአረግ የተቀበሉት መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ለሁሉም ማህበረሰብ የሚለውን የአልማ አታ ዲክላሬሽን ዓለም አቀፋዊ ስምምነት ሆኖ እንዲተገበር  ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከነበራቸው የቀድሞ የካዛኪስታን ጤና ሚኒስቴር ፕሮፌሰር ሻርማኖቭ እጅ መሆኑን በማህበራዊ የትስስር ገፃቸው ላይ አጋርተዋል፡፡

ፕሮፌሰሩ በጤናው ዘርፍ ላይ ለጋሲያቸውን ለአለም ማህበረሰብ በማበርከታቸው ከፍተኛ ምስጋና እንዳላቸው ዶ/ር ቴድሮስ በማህበራዊ ትስስራቸው ላይ አስፍረዋል፡፡

የአልማ አታ ዲክላሽን ተደራሽነት መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ለሁሉም የሚለው ለሰዎች ጤና መጠበቅ መሰረታዊ መሆኑን የጠቀሱት የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳሬክተሩ፣ የካዛኪሰታን ጤና ሚኒስትር ዶክተር አዝሃር ጊኒያት መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ለማዳረስ እየሰጡት ያለውን አመራርና ጥበብ አመስግነዋል፡፡

የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሐኖም በጤና ዘርፍ ለአለም ማህበረሰብ እያበረከቱት ያለውን ሙያዊ አስተዋፅኦና የአመራር ጥበብ ከስኮትላንድ ኤደን በርግ ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ሽልማት ተበርክቶላቸው እንደነበር ይታወሳል።

ዶ/ር ቴድሮስ አድሐኖም የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳሬክተር ሆነው እያበረከቱት ያለውን የአመራር ብቃት በማድነቅ በያዝነው አመት የክብር ማአረግ ሲሰጣቸው የአሁኑ ለሶስትኛ ጊዜ ነው።

በተመሳሳይ ዶ/ር ተድሮስ ኡቡንቱ የተሰኘ የሰብአዊነት የክብር ሽልማት ከደቡብ አፍሪካ መሸለማቸው የሚታወስ ነው።